እግር ሲጥል

June 30th, 2008 by Brango

ዕለቱ እሁድ ነው:: ጠዋት ከንቅልፌ ነቃሁና ገላዬን ተለቃልቄ ለሳምንት ከምቆይበት ከባለ አምስት ኮከቡ ሆቴል ፕሮቪደንስ ወጥቼ ቁርስ ለመብላት ወደ አንድ ካፌ አመራሁ::

***

የጠዋቷ ፀሐይ እየተንቦገቦገች ነው:: ራሷ ውበትን ተጎናጽፋ አካባቢውን ውበት አጎናጽፋዋለች:: በፈረንጆቹ አቆጣጠር 2007 የሰኔ ወር መጨረሻ ላይ:: ፕሮቪደንስ ሮድ አይላንድ:: ፕሮቪደንስ ከቦስተን ማሳቹሴትስ ብዙም ርቃ የማትገኝ በተለይ ክረምት ላይ የምትደራ አሜሪካ ውስጥ የምትገኝ መካከለኛ ስፋት ያላት ከተማ ናት:: የብራውን ዩኒቨርስቲ በከተማዋ ውስጥ መገኘት ይበልጥ አድምቋታል:: ተማሪዎችም ብዙውን ጊዜ ሳትወድ በግድ ያደምቋታል—በረዶ እየዘነበም ቢሆን:: ተማሪነት ከትኩስ ወጣትነት ጋር ተዳምሮ ለከተማዋ ልዩ እስትፋንሷ ነው—ልዩ ውበቷ! ፕሮቪደንስ የጥበብ ሥራዎችም መፍለቂያ ናት:: ጥሩ ሆቴሎችና ሬስቶራንቶችም አሉ:: ካፌዎችም እንዲሁ:- ከግዙፉ እስታርባክስ እስከ ትንጥዬዋ ካፌ ሉና! እሱ ትላልቅ ሆቴሎች ውስጥ ከመመገብ ትናንሾቹ ጋር መመገብን ይመርጣል:: ትናንት ቁርሱን ካፌ ሉና እራቱን ደግሞ ማይ ሊትል ፍሬንች ኮቴጅ በሚባል ሬስቶራንት ውስጥ ተመግቧል:: ምሳ ሥራ ቦታ ላይ ሆኖ ነው የበላው:: እሱ ለምሳ ብዙም አይጨነቅም:: ቀለል ያለ ሳንድዊችን ያዘወትራል:: ወይም ደግሞ የአትክልት ሳላድ:: የኢትዮጵያ ሬስቶራንት ፕሮቪደንስ ውስጥ አላጋጠመውም:: እዚህች ከተማ ውስጥ ለአንድ ሳምንት ያህል ይቆያል:: ከኮሌጅ ከተመረቀ ሁለት ወር ሊሞላው ጥቂት ቀናት ናቸው የቀሩት:: ዕድለኛነቱ ወዲያው እንደተመረቀ ሥራ ለመያዝ መቻሉ:: ለነገሩ ይህን ሥራ የጀመረው ተማሪ ሳለ ነበር—ኢንተርን በመሆን:: ሥራው ብዙ መጓዝን ይጠይቃል:: የሚሰራበት ካምፓኒ ሁሉንም ወጪ እየከፈለ ከቦታ ቦታ ይልከዋል:: የሱ ሀላፊነት ካምፓኒውን ማስተዋወቅና ከሌሎች ተመሳሳይ ካምፓኒዎች ጋር ግንኙነትን መፍጠር ነው:: ባለ አራትና ባለ አምስት ኮከብ ሆቴሎች ውስጥ በየጊዜው ማረፍ ሳይሰለቸው አይቀርም:: ምንም እንኳ ባረፈበት ሆቴል ቁርስ መብላት ቢችልም ብዙን ጊዜ የትላልቅ ሆቴሎች ቁርስ አይመቸውም::

***

ሁለት ቀን ካፌ ሉና ቁርሴን ስለበላሁ ዛሬ ደግሞ እስኪ ሌላ ቦታ ልሞክር አልኩና ወደ ካፌ ላ ፍራንስ አቀናሁ:: የፈረንሳዮችን ቁርስ ናፍቄ ሳይሆን በቃ አዲስ ነገር ለመሞከር:: ፍሬንች ቶስት ከካፌ ሞካ ጋር አዝዤ ጥጉ ላይ ወንበር ስቤ ቁጭ አልኩ:: አይፖዴን ከኪሴ አወጣሁና “ቫዮለንትሊ ሃፒ” የተሰኘውን የብዮርክን ሙዚቃ ማዳመጥ ጀመርኩ:: ጠዋቱን እንዲህ ካልጀመርኩት አይቻልም:: ዕለቱ እሁድ ቢሆንም ከሁለት ሰዓት በሁዋላ ሃይለኛ ስብሰባ አለብኝ:: ማታ ስዘጋጅበት ነበር:: የፓወር ፖይንቴን ደጋግሜ አጥንቼዋለሁ:: የ20 ደቂቃ ፕረዘንቴሽን አቀርባለሁ ለተለያዩ የቢዝነስ ማናጀሮች:: ይህ ሥራ ምንም እንኳ ልቤ ፈቅዶት የምሰራው ነገር ባይሆንም ጥሩ ስለሚከፈለኝ ቀን ማታ አዘቦት ሰንበት ሳልል እለፋበታለሁ:: ፍላጎቴ ግን ያለው ሌላ ቦታ ነው::

ቁርሴን እየበላሁ የብዮርክን ሙዚቃ እየመላለስኩ አዳመጥኩት:: አንድን ዘፈን ከወደድኩት መላልሼ ማዳመጥ ደስ ይለኛል:: ስልችት ሲለኝ ደግሞ እርግፍ አደርገውና ለወር ለሁለት ወር ያን ዘፈን ዞር ብዬ አላየውም:: በጣቶቼ ክቡን ጠረጴዛ እየቆረቆረኩ ካፌ ሞካውን አጣጣምኩት:: ካፌ ሞካ በቅርቡ ፍቅር ካስያዙኝ ነገሮች መካከል አንዱ ነው:: የራሱ የሆነ ታሪክ አለው:: ዝርዝር ውስጥ አልገባም::

ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ህይወቴን ለዘላለሙ የሚለውጥ ነገር ተከሰተ::

ከፊት ለፊቴ አንድ የፀሐያ መነጽር ያጠለቀ ጺማም ነጭ ቁጭ ብሏል:: ያዘዘው ዳቦና ውሃ ነው:: የሚገርም! አልኩኝ በልቤ:: ደረቁን ዳቦ እየቆረሰ ይበላል:: ቆይቶ ደግሞ በውሃ ያወራርደዋል:: አልፎ አልፎ ገልመጥ ያደርገኛል:: ብዙ ስላየሁት መሰለኝ:: “ማይንድ ዩር ኦውን ቢዝነስ!” ዓይነት ነገር ነው አስተያየቱ:: ሆኖም እሱን ከመታዘብ አልተቆጠብኩም:: በጣቶቼም የማዳምጠውን ሙዚቃ ምት እየተከተልኩ ጠረጴዛውን መቆርቆሩንም እንዲሁ:: በስተግራዬ ደግሞ አንድ ነጭና አንዲት ኬንያዊ የምትመስል ቆንጆ ልጅ ቁጭ ብለዋል:: ሁለቱም መጽሃፍ በጃቸው ይዘዋል:: ትኩስ ቡና ፉት እያሉ ይወያያሉ:: እሷ በቦዲና ፒጃማ ነው ያለችው:: ከንቅልፏ እንደ ነቃች ወደ ካፌው ያመራች ትመስላለች:: ጡቶቿ ቦዲዋን ቀደው ለመውጣት የሚታገሉ ይመስላሉ:: አፍንጫዋ ትንሽዬ ናት:: ጸጉሯ ድሬድ ሎክ ነው:: በስተቀኜ ደግሞ አንድ በጣም ወፍራም ነጭ ሴትዮ ትልቅ የአሳማ ሥጋ ያለበት ሳንድዊች እየገመጠች ነው:: ከበስተጀርባዬ ሁለት ኢትዮጵያዊያን ቁጭ ብለዋል:: ላናግራቸው አሰብኩና በወሬያቸው መሀል ጣልቃ ከምገባስ ይቅርብኝ ብዬ አለፍኳቸው::

ያ ዳቦ በውሃ ሲመገብ የነበረ በድሜው ገፋ ያለ ጺማም ነጭ ወደ ተቀመጥኩበት ጠረጴዛ መጣ:: አንዲት መጽሐፍ የሱሬው ኪስ ውስጥ ውትፍ አድርጓል:: ያናግረኝ ጀመር:: የሙዚቃ ማዳመጫውን ጆሮዬ ላይ ሰክቼ ስለነበር ምን እንዳለኝ አልሰማሁትም:: እናም ማዳመጫውን ከጆሮዬ ላይ ነቀልኩት:: “ይቅርታ አልሰማሁህም” አልኩት በፈረንጅኛ:: “ምን ዓይነት ሙዚቃ እንደምታዳምጥ ነበር የጠየቅኩህ” አለኝ መነጽሩን እያወለቀ:: በጥያቄው ግራ ብጋባም “ብዮርክን ነው የማዳምጠው” አልኩት:: “የአይስላንድዋን ንግስት?! በጣም ግሩም ዘፋኝ ናት:: አንተም ስሜታዊ ሆነህ በጣቶችህ የሐሳብ ፒያኖን እየመታህ እያዳመጥካት ነው:: ግሩም!” አለና መለሰልኝ:: “የሙዚቃ መሳሪያ ትጫወታለህ?” ብሎ ከጠየቀኝ በኋላ ወንበር ስቦ ቁጭ አለ:: የኔን ፈቃድ አልጠየቀም:: ጤነኛ ነው እንዴ ሰውየው? እያልኩኝ በሆዴ “አይ የሙዚቃ መሳሪያ አልጫወትም:: ነገር ግን ለመጫወት በጣም እፈልጋለሁ:: በህይወቴ በጣም የምመኘው ነገር ነው!” አልኩት:: “መጀመሪያ ምኞት ይቀድማል:: ምኞት የሁሉም ነገር በር ከፋች ነው:: ከዚያም እንግዲህ እንደባለቤቱ ሁኔታ ምኞት ወይ ይሳካል አልያም ምኞት ሆኖ እውነት ሳይሆን ይቀራል::” በማለት መለሰ:: “እኔም እንዳንተ እመኝ ነበር::” በማለትም ቀጠለ:: “ምን ዓይነት ምኞት?” ጠየቅሁት::

“ዌል … ልክ እንዳንተው የሙዚቃ መሳሪያ የመጫወት ምኞት::”
“ምን ዓይነት የሙዚቃ መሳሪያ?”
“ፒያኖ!”
“ህምምም … ታዲያ ምኞትህ እውን ሆነልህ?”
“በሚገባ! አንድ ቀን ከአንድ ጀርመናዊ ጋር ተዋወቅሁኝ:: የት ተገናኘን መሰለህ? አንዲት ምናምንቴ ካፌ ውስጥ:: በዚያ ሰዓት እንደ አንተ አይፖድ የማዳመጥ እድሉ አልነበረኝም:: ሆኖም ካፌው ውስጥ ሲጫወት የነበረውን ሙዚቃ እያዳመጥኩ በጣቶቼ የምመገብበትን ጠረጴዛ ስቆረቁር ጀርመናዊው አስተዋለኝ:: እናም ቀረበኝ:: አነጋገረኝ:: ማን እንደ ሆነ ምን እንደሚሰራ ከገለጸልኝ በኋላ ህይወቴን ለዘላለሙ የሚቀይር ነገር አደረገልኝ:: ምኞቴ ተሳካ:: ህልሜ እውን ሆነ:: ጀርመናዊው ሰው ከሙዚቃ ጋር አስተዋወቀኝ:: ስሙ ፍራንዝ ሉድዊግ ይባል ነበር—ነብሱን ይማርና:: የፒያኖ ማስተር መሆኑን የተረዳሁት በሥሩ ትምህርቴን መከታተል ከጀምርኩ በኋላ ነበር:: ታዋቂ የፒያኖ ተጫዋችና የዩኒቨርስቲ ፕሮፌሰር ነበር:: ራሱን ሲያስተዋውቀኝ ግን ብዙም ስለ እውቅናው አልነገረኝም:: ህይወቱ ልታልፍ ስትል ቃል አስገባኝ:: ልክ እሱ እውቀቱን ለኔ እንዳጋራ ሁሉ እኔም ለአንድ ሰው እውቀቴን እንዳጋራ:: ያ እውቀቴን የማጋራው ሰው በአጋጣሚ የምገናኘውና የሌላ ሀገር ዜጋ ሆኖ ለሙዚቃ ልዩ ፍቅር ያለው መሆን እንዳለበትም ገለጸልኝ:: የዛሬ 40 ዓመት ነበር ይሄ የተከሰተው::”
“በጣም የሚገርም ታሪክ ነው:: የየት ሃገር ሰው ነህ—ማለቴ ትውልድህ:: እዚሁ አሜሪካ ውስጥ ነው?”
“ኦህ ኖ … ፈረንሳይ ነው የተወለድኩት:: ጀርመናዊውን የተዋወቅሁት እንግሊዝ ውስጥ ነበር:: ያጋጣሚ ነገር ሆነና ወደዚህ ሀገር ፈለስኩ:: አንተስ የየት ሃገር ሰው ነህ?”
“እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ:: ግን ለጊዜው ነው እዚህ የምኖረው:: ለትምህርት ነበር የመጣሁት:: ትምህርቴን ጨርሼ አሁን በመስራት ላይ ነኝ—ለአንድ የማስታወቂያ ድርጅት::”
“በጣም ግሩም:: ቀጣዩ ዕቅድህ ምንድነው?”
“እርግጠኛ አይደለሁም:: ትምህርቴን የጨረስኩት በቅርቡ ነው:: አሁን በምሰራበት ሞያ የምቀጥል አይመስለኝም:: ፍላጎቴ ያለው ሌላ ቦታ ነው:: ሙዚቃ ላይ! በተለይም ስለፒያኖ መማር በጣም እፈልጋለሁ:: የሚያሳዝነኝ ነገር ግን የሙዚቃ ትምህርት ቤት መግባት የምችል አይመስለኝም ከዚህ በኋላ:: ላለፉት አራት አመታት ያጠናሁት የቢዝነስ ትምህርትን ነበር:: ሁለት የሙዚቃ ኮርሶችን ከመውስድ ውጪ ብዙም ስለሙዚቃ የማውቀው ነገር የለኝም:: እናም በዚህ ምክንያት ወደ ሙዚቃ ትምህርት ቤት የመግባት ህልሜ በጣም የሞተ ነው:: ነገር ግን ሙዚቃን ማወቅ ዛሬም ቢሆን ከልቤ የምመኘው ነገር ነው::”
“ብዙም ተስፋ አትቁረጥ:: እንዳልኩህ ሁሉም ነገር በምኞት ይጀምራል:: ዕድል ምኞትህን ለማሳካት የቤትህን ደጃፍ ስታንኳኳ በፍንደቃ ኖር ማለት ነው:: ምን ዓይነት ሙዚቃ ትወዳለህ?”
“እኔ በርግጥ ይህ ነው ብዬ የምለየው ሙዚቃ ባይኖርም ከክላሲካል ሙዚቃ የቤቶቨንን የሾፐንን እንዲሁም የኢትዮጵያዊቷን የእማሆይ ጽጌ ማርያም ገብሩን ሙዚቃ በጣም እወዳለሁ:: ከሌላ የሙዚቃ ዘርፍ ደግሞ የጃዝ የሬጌ የሳልሳ የሜሬንጌ የብሉና የአፍሮቢት እንዲሁም የኢንዲ ሙዚቃ ነብሴ ነው:: የተለያዩ ሀገሮች ሙዚቃንም ማዳመጥ አዘወትራለሁ — ለምሳሌ የመካከለኛው ምስራቅንና የህንድን ሙዚቃ:: የሀገሬ ሙዚቃ ደግሞ ከሁሉም በላይ ይስማማኛል::”
“ጥሩ ምርጫ ነው:: ሙዚቀኛ ለመሆን ብዙ የሚጎልህ ነገር የለም:: ተሰጦውም ሊኖርህ ይችላል:: ማን ያውቃል?! በተለይ የሀገርህን ሙዚቃ አብልጠህ መውደድህ ደግሞ ግሩም የሚያሰኝ ነው:: እማሆይ ጽጌ ያልካቸውን ሙዚቀኛ አውቃቸዋለሁ:: ማለቴ ሙዚቃቸውን አዳምጫለሁ:: ስራቸው ረቂቅ ነው:: የእሳቸውን እግር መከተል የምትፈልግ ከሆነ ከአንተ ፈቃድ ጋር ባስተምርህ ደስ ይለኛል::”
“አር ዩ ሲርየስ?!”
“በሚገባ! ብራውን ዩኒቨርስቲ ውስጥ የሙዚቃ ትምህርት አስተማሪ ነኝ:: የማተኩረው ክላሲካል ፒያኖ ላይ ሲሆን ሳክስፎንም አስተምራለሁ:: ፍላጎቱ ካለህ እኔ አንተን ለማስተማር ዝግጁ ነኝ::”
“ግን እንዴት ሊሆን ይችላል:: ለምን እኔ?”
“ዚስ ሜይ ሳውንድ ዊርድ:: ግን አየህ ያ መምህሬ ቃል አስገብቶኛል:: እስከዛሬ ብዙ ሰዎች አጋጥመውኛል:: አብዛኛዎቹ ሙዚቃ ለመማር እንደሚፈልጉ ቢገልጹልኝም በቃላቸው ጸንተው አላገኘሁዋቸውም:: እስከዛሬ ብቁ የሆነ የፒያኖ ተማሪ አልፈጠርኩም:: ከኔ የተሻለ የፒያኖ ተጫዋች መፍጠር እፈልጋለሁ:: ሳይህ አንተ ጥሩ እጩ ትመስለኛለህ:: አላየኸኝ ይሆናል እንጂ እዚህ ካፌ ውስጥ ከገባህበት ሰዓት አንስቶ ሁኔታህን ስከታተል ነበር:: ጥቁር ብትሆንም የኔን ወጣትነት በጣም ነው ያስታወስከኝ:: እንዳንተ ቀጠን ያልኩ ነበርኩ:: ጠረጴዛ መቆርቆር በጣም እወዳለሁ:: ቁርስ ላይ ፍሬንች ቶስትና እና ካፌ ሞካ ነበር የማዘወትረው እስከቅርብ ጊዜ ድረስ:: ዛሬ ግን ሁኔታዎች ተለውጠው ደረቅ ዳቦ እመገባለሁ:: ኤንዌ ኢፍ ዩ አር ሲርየስ ቱ ለርን ሚውዚክ ማይ ዶር ኢዝ ኦፐን ፎር ዩ:: ማይ ዋፍይ ዊል ቢ ቬሪ ግላድ ቱ ሲ ዩ ኤንድ ጌት ቱ ኖው ዩ:: ሳራፊና ትባላለች:: ከደቡብ አፍሪካ ነች:: የቤት ቁጥራችን ይኸውልህ:: ካም ሲ ኣስ ኦር ጊቭ ኣስ ኧ ኮል::” ብሎ ካርዱን ሰጥቶኝ ተሰናብቶኝ ወጣ::

ግራ የሚያጋባ ነገር ሆነብኝ:: እሺም እምቢም የማይሉት ነገር:: አሁን ምን ላደርግ ነው? አንድን ነጭ አምኜ ሥራዬን ልተው? ፈርቼስ ደጅ አንኳኩቶ የመጣልኝን ዕድል ላልፍ? የትኛው መንገድ እንደሚያዋጣኝ በግልጽ አላውቅም::

***

በሳምንቱ መጨረሻ ላይ እሱ በአንድ አቋም ጸና:: የሙዚቃውን ፕሮፌሰር ሄዶ ለማየት ወሰነ:: የጀመረውን የሥራ ኩንትራት እስኪፈጽም ድረስ ፕሮፌሰሩ በትዕግስት እንዲጠብቀውም ተማፀነው:: ፕሮፌሰሩ ፈቀደለትም::

አንዳንድ አጋጣሚዎች ይገርማሉ:: ከአንድ ዓመት በኋላ እሱ የሙዚቃ ተማሪ ሆኖ ትምህርቱን በመከታተል ላይ ይገኛል:: ቪዛን በተመለከተም ችግር የለበትም:: የተማሪነት የመኖርያ ፈቃዱ ተራዝሞለታል:: በቅርቡ እማሆይ ጽጌ ማርያም ገብሩን ለመገናኘት ወደ እየሩሳሌም ያቀናል:: ለማመን የሚያስቸግር እውነታ ማለት እንደዚህ ዓይነቱን ነው:: ላይፍ ኢዝ ፉል ኦፍ ሰርፕራይዝስ! የማይቻል ነገር የለም::

ተይ ባክሽን!

June 26th, 2008 by Brango

ስለ ወደድኩሽ፣ ምንድነው ምትይኝ?
ስላፈቀርኩሽ፣ ምንድነው ምትይኝ?
ተይ! ባክሽን፣ አትኩራሪብኝ!
ተይ! ባክሽን፣ አትዝናኚብኝ!

ማነሽ፣ ተናገሪ፣ አንቺ የደም ገንቦ?
ልቤን አማለለው፣ ውበትሽ አብቦ።
ካይኔ ገብተሻል፣ ልታስ-ጨንቂኝ፤
ለማታመልጪኝ፣ ተይ አታሩጭኝ!

“ወደድኩሽ” ስልሽ፣ ፉተታ አይደለም፤
ከምሬን ነውና፣ ነይልኝ የኔያለም።
አህ! አንቺ ልጅ፣ ተይ ስሚኝ!
ተይ! አንቺ ልጅ፣ ቅረቢኝ!

ዓይኖቼ ጓጉ፣ ዓይተው ዓይንሽን፤
ልቤም ዘለለ፣ ወዶ ልብሽን፤
አካሄድሽን፣ ወድ-ጄዋለሁ፤
ባረማመድሽ፣ ተማር-ክያለሁ።

ስለወደድኩሽ፣ ምንድነው ምትይኝ?
ስላፈቀርኩሽ፣ ምንድነው ምትይኝ?
አንቺ ቆንጆ፣ ተይ አትሽሽኝ!
ሮማኔ ሆይ፣ ችላ አትበይኝ!

እንደማልሆንሽ፣ በምን አወቅሽው?
ቆንጂት ቀርበሽኝ፣ ውስጤን ሳታይው፣
“ሰው አለኝ” እያልሽ፣ የምትዋሽው፣
ምን በድዬሽ ነው፣ የምትርቂው?

አህ!
አህ! አህ!
አህህህህህህህህህህ!

አህ! አንቺ ልጅ፣ ተይ ስሚኝ!
ተይ! አንቺ ልጅ፣ ቅረቢኝ!
ተይ! አንቺዬ፣ ውደጂኝ!
ጡር ነውና፣ አትግፊኝ!

ተይ! ተይ! ተይ!
ተይ! ተይ!
ተይ!

Inspired by this song.

ትራጄዲያዊ ሞት

June 24th, 2008 by Brango

ትራጄዲያዊ ሞት፣
ያልፍልኛል ብሎ፣
ከናት ሀገር ርቆ፣
በሰው ሀገር መቅረት።
ትራጄዲያዊ ሞት፣
መሆን የእሳት እራት፤
የላብራቶር ዕቃ፣
በማያውቁት መሬት፤
ወይም በቃሬዛ፣
ተጭኖ ወዳገር ቤት፤
ምኞት ሳይሳካ፣
ሳይሞላ ባዶ ቤት፣
ከዚች ዓለም መጥፋት፤
ህልምም ሳይፈታ፣
ወደ መቃብር ቤት።
“እማዬ፣ አባዬ፣
ወንድም፣ እህትዬ፣
ልሞት ነው ናፍቃችሁኝ፤
ኑና አይዞሽ በሉኝ!
ኑና አይዞህ በሉኝ!”
እየተጫጫረ፣
ህይወት ባጭር ቀረ።
ትራጄዲያዊ ሞት፣
በለጋ ዕድሜ መቀጨት፤
መበደል፣
መገደል፣
ያውም በሀገር ልጅ፣
በሚያውቁት ሰው እጅ!

ሲጋራ

June 23rd, 2008 by Brango

ሳስቶ ልቤ፣ አጨስሃለው፤
አጨስሃለው!
ጠቁሮ ሣንባዬ፣ እምግሃለው፤
እምግሃለው!
በዱቤም ቢሆን፣ እስብሃለው፤
እስብሃለው!

ሲጋራ፣ ሲጋራ፣ ሲጋራ፣
ወደፊት፣ ወደፊት፣ ካንተ ጋራ!

ሲጋራ፣ ሲጋራ፣ ሲጋራ፣
ያንተ ፍቅር፣ ኪሳራ፣ ኪሳራ!

ገምቶ አፌ፣ አጨስሃለው፤
አጨስሃለው!
ከስሎ ጥርሴ፣ እምግሃለው፤
እምግሃለው!
ጎጆዬም ፈርሶ፣ እስብሃለው፤
እስብሃለው!

ሲጋራ፣ ሲጋራ፣ ሲጋራ፣
በሱስ ስም፣ ተውማ፣ ግፍ አትስራ!

ሲጋራ፣ ሲጋራ፣ ሲጋራ፣
ያንተ ፍቅር፣ ስቃይ ነው መከራ!

ተበቀልልኝ ብዬ፣ ንዴት፣ ብስጭትን፣
መጠጥኩት፣ ሳልሰስት፣ ፊልተሩን።

ፊልተሩም፣ ወደ ውስጥ በመግባት፣
መጠጠው፣ የሣንባዬን ውበት።

ጥላሸት ቀብቶ፣ ቀባብቶ፣
ውስጤን አከረፋው፣ ሲጋራው አግምቶ።

ሲጋራ፣ ሲጋራ፣ ሲጋራ፣
መልከ ጥፉ፣ የካንሰር አዝመራ!

ሲጋራ፣ ሲጋራ፣ ሲጋራ፣
አመለጥኩህ፣ እኔን ጉድ ሳትሰራ።

ቂ! ቂ! ቂ! ቂ! ቂ! ቂ! ቂ!

የአብራሃም ዘር ነፍስ ቃል

June 22nd, 2008 by Brango

ነአኩተከን ልድገም፣ ምስጋናዬን ላቅርብ፣
ሁሉን ላደረገ፣ ስሙ ለማይጠገብ።

አልሃምዱሊላሂ፣ ህይወቴን ባረከው፣
ከማመስገን ውጪ፣ የለኝም የምለው።

ገለታ ዋቀዮ፣ ተመስገን ጎይታና፣
ግራሲያስ አ ዲዮስ፣ ክብርና ምስጋና!

በሚገባኝ ቋንቋ፣ ምስጋና አቀርባለሁ፣
ማን ይቃወመኛል፣ ጮኼም ዘምራለሁ?!

ያ ረቢ፣ ያ አላህ፣ አዶናይ፣ አምላኬ፣
ለኔ ምን ሊፈይድ፣ ካንተ ሌላ አምልኬ?

ተመስገን፣ ተመስገን፣ ተመሰገን ዘላለም፣
በዳዊት እንዚራ፣ በሱፊዎች ዜማም።

ብርሃንን ላሳየኝ፣ ከጨለማ አውጥቶ፣
ምስጋናዬ ብዙ፣ ለሰጠኝ አብዝቶ።

በኔ በደቃቃው፣ በትንሽ ጅላጅል፣
ተመስገን ጌታዬ፣ እስትንፋሴና ቃል።

ለምን አያነቡ ዓይኖች?

June 20th, 2008 by Brango

የናት ጡት ደርቆባቸው፣
ህይወት ከፍታባቸው፣
ዋይ፣ ዋይ ሲሉ ህጻኖች፣
ለምን አያነቡ ዓይኖች?

ማሙሽ፣ ሚሚን የሚያስነባ፣
ረሐብ ክፉ፣ ጥላ አልባ።
እናት፣ ልጅን የሚለያይ፣
ረሐብ ክፉ፣ የሚያሰቃይ።
ሀገር፣ ወገን የሚያቃውስ፣
ረሐብ ክፉ፣ የሚያረክስ።

የኔም ዓይን፣ ሲያይ ፎቶ፣
ልቤ አነባ፣ ዘፈን ሰምቶ፤
“ዋይ፣ ዋይ፣ ዋይ ሲሉ፣
የረሐብን ጉንፋን ሲስሉ፣
እያዘንኩኝ ባይኔ አይቼ፣
ምን ላድርግ ?
አለፍኳቸው ትቼ!”

አይዞን

June 18th, 2008 by Brango

አይዞን!

አይዞን!

አይዞን! አይዞን!

“አይዞህ!”፣ “አይዞህ!” ይሉኛል፤

“አይዞህ!”

እኔ ግራ ገብቶኛል፤
“አይዞህ!”

“አይዞህ” ማለት ምንድነው፣

ፍቅር ሲሸሽ እያየሁ?

አይዞህ ማለት ምንድነው፣
ክፉ ወሬ እየሰማሁ?


“አይዞህ!”፣
”አይዞህ!” ትላለች፤
“አይዞህ!”
የምሆነውን አጣሁ፤
“አይዞህ!”

“አይዞህ!”፣
”አይዞህ!” ይለኛል፤
“አይዞህ!”
ጥበብንም ተጠማሁ፤

“አይዞህ!”

“አይዞን!” በቂ አይደለም፤
ልቤ ሲሞት፣
 ሲገደል።

“አይዞን!” በቂ አይደለም፤

ልቤ ሲጋይ፣ ሲቃጠል።

“አይዞህ!”፣ “አይዞህ!” ይሉኛል፤

“አይዞህ!”
“ሁሉ ያልፋል!” ይሉኛል፤


“አይዞህ!”

ራሴ ራሴን ስበድል፣

“አይዞህ!”

ሌላው እኔን ሲበድል፣

“አይዞህ!”

“አይዞህ!” ማለት ምንድነው፣

ፍቅር ልቤን ሲጎዳው?

“አይዞህ!” ማለት ምንድነው፣

ጥቁረት ቤቴን ሲወረው?

“አይዞህ!” ማለት ምንድነው፣

ሆዴን ሆድ እየባሰው?

“አይዞን!” እያላችሁኝ፣ 

“አይዞህ!”

ሰዎች አታባብሉኝ፤


“አይዞህ!”

ኑና ልቤን እዩልኝ፤

“አይዞህ!”

አሯል፣ እሣት በልቶብኝ፤
“አይዞህ!”

“አይዞህ!”፣ “አይዞህ!” ይሉኛል፤

ሰዎች ያባብሉኛል።

“አይዞህ!” ማለት ምንድነው፣ 

ሰው ሞት እየናፈቀው?

“አይዞህ!”፣ “አይዞህ!” እያሉ፣
“አይዞህ!”

ሰዎች ያታልሉኛል፤
“አይዞህ!”

ፍቅር ጠፍቶ እያዩ፣
“አይዞህ!”

“ሀገር ሰላም!” ይሉኛል፤
“አይዞህ!”

“አይዞን!”፣ “አይዞን!” እያለች፣

እሷ ልቤ ውስጥ ገባች።
የቀንዋ ፀሐይ ጠፍታ፣
የምሽት ኮከብ በራች።

“አይዞህ!”፣ “አይዞህ!” ይሉኛል፤
“አይዞኝ!”

አይዞህ ይናፍቀኛል፤
“አይዞኝ!”


“አይዞህ!” ማለት ምንድነው?
“አይዞህ!” ማለት ጥሩ ነው።

አይዞን!
አይዞን!

አይዞን!
አይዞን!

ሳልወደው ወድጄው

June 18th, 2008 by Brango

ሳልወደው ወድጄው ልቤ ቢባዝንም
ከንግዲህ በቅቶኛል ጊዜ አላባክንም

ልቤን ብከፍትለት የሚገባ መስሎኝ
ወደደቺኝ ብሎ ጉራውን ነዛብኝ

ይብላኝ እንጂ ለሱ በሩን ዘግቻለሁ
መጥቶ የሚያንኳኳ እኔ መቼ አጣሁ

ለመሞከር እንጂ ድሮም አልወደድኩት
እሱ ግን ተሞኘ የከነፍኩኝ መስሎት

ሰው ዓሳ ሊያጠምድ ባህር ዳር ይሄዳል
አንዱ ካመለጠው ሌላ ይመጣለታል

ታዳኞች እስካሉ አዳኞች አይጠፉም
እሱን እያሰብኩኝ ጊዜዬን አልገልም